በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡
ቁርኣን 2፥223 ሴቶቻችሁ ለእናንተ እርሻ ናቸው፥ እርሻችሁንም በፈለጋችሁት ኹኔታ ድረሱ፡፡
نِسَاؤُكُمْ حَرْثٌ لَّكُمْ فَأْتُوا حَرْثَكُمْ أَنَّىٰ شِئْتُمْ
በቁርኣን አምላካችን አሏህ ወንድ ለሴት "ልብስ" እንደሆነ እንዲሁ ሴት ለወንድ "ልብስ" እንደሆነች ይነግረናል፦
ቁርኣን 2፥187 በጾም ሌሊት ወደ ሴቶቻችሁ መድረስ ለእናንተ ተፈቀደላችሁ፡፡ እነርሱ ለእናንተ ልብሶች ናቸው፥ እናንተም ለእነርሱ ልብሶች ናችሁ፡፡
أُحِلَّ لَكُمْ لَيْلَةَ الصِّيَامِ الرَّفَثُ إِلَىٰ نِسَائِكُمْ ۚ هُنَّ لِبَاسٌ لَّكُمْ وَأَنتُمْ لِبَاسٌ لَّهُن
እዚህ አንቀጽ ላይ ወንድ ለሴት ሴት ለወንድ "ልብስ" ናቸው ሲል በፍካሬአዊ ሃፍረትን፣ ነውርን እና ገበናን "መሸፈኛ" ማለት እንጂ በእማሬአዊ ወስዶ "ጃኬት" ወይም "ቀሚስ" አሊያም "ሱሪ" ማለት አይደለም። በተመሳሳይ ሴት ለወንድ እርሻ ናት፦
ቁርኣን 2፥223 ሴቶቻችሁ ለእናንተ እርሻ ናቸው፥ እርሻችሁንም በፈለጋችሁት ኹኔታ ድረሱ፡፡
نِسَاؤُكُمْ حَرْثٌ لَّكُمْ فَأْتُوا حَرْثَكُمْ أَنَّىٰ شِئْتُمْ
መቼም ቂል የሆነ ሰው ካልሆነ ሴት ለወንድ "እርሻ" ናት ሲባል ሞፈርና ቀንበር አዋዶ የሆነው የጓሮ አትክልት አሊያም ሰብል ናት ማለት እንዳልሆነ እሙንና ቅቡል ነው፥ ቃሉ የወከለው እሳቤ እማሬአዊ ሳይሆን ፍካሬአዊ ነው። የሴት ልጅ ማኅፀን ዘር የሚዘራበት "እርሻ" ሲመሰል የእንሥት ማህፀን ላይ ላይ የሚገናኘው የተባእት ዘር ሕዋስ ደግሞ ገበሬ እርሻ ላይ በሚዘራው "ዘር" ተመስሏል፥ ወንድ ዘሩን ዘሪ ሲሆን ሴት ያንን ዘር የምታፈራበት እርሻ ናት። ምክንያቱም አንድ ገበሬ እርሻው ላይ ከዘራ በኃላ ዘሩ ዳብሮ ለፍሬ የሚበቃው በእርሻ ውስጥ እንደሆነ ሁሉ አንድ ተባእትም አንድ እንስት ማኅፀን ውስጥ ዘሩን ተገናኝ ሆኖ ከዘራ በኃላ ሂደቱ ሁሉ ተከናውኖ ለፍሬ የሚበቃው ማኅፀን ውስጥ ስለሆነ ነው። በማኅፀን ውስጥ በመፍሰስ የሚዘራው ዘር የተንጣለለ ደካማ ውኃ የሆነው የፍትወት ሕዋስ ነው፥ ይህም ሕዋስ በተጠበቀ መርጊያ በእርሻው ውስጥ ለፍሬ እስኪበቃ ይቆያል፦
ቁርኣን 56፥58 በማኅፀኖች የምታፈሱትን አያችሁን?
أَفَرَأَيْتُم مَّا تُمْنُونَ
ቁርኣን 56፥63 የምትዘሩትንም አያችሁን?
أَفَرَأَيْتُم مَّا تَحْرُثُون
ቁርኣን 32፥8 ከዚያም ዘሮቹን ከተንጣለለ ከደካማ ውኃ ያደረገ ነው፡፡
ثُمَّ جَعَلَ نَسْلَهُ مِن سُلَالَةٍ مِّن مَّاءٍ مَّهِينٍ
ቁርኣን 23፥13 ከዚያም በተጠበቀ መርጊያ ውስጥ የፍትወት ጠብታ አደረግነው፡፡
ثُمَّ جَعَلْنَاهُ نُطْفَةً فِي قَرَارٍ مَّكِينٍ
ታላቁ የቁርኣን ሙፈሢር ኢብኑ ከሲር የኢብኑ ዐባሥን ንግግር ዋቢ በማድረግ የፈሠሩት በዚህ መልክ እና ልክ ነው፦
ተፍሢሩል ኢብኑ ከሲር 2፥223
ንግግሩ፦ "ሴቶቻችሁ ለእናንተ እርሻ ናቸው" የሚለውን ኢብኑ ዐባሥ፦ "እርሻ የሚለው የእርግዝናን ቦታ ነው”" ብሏል"።
وقوله : ( نساؤكم حرث لكم ) قال ابن عباس : الحرث موضع الولد
"ሴት" እና "ወንድ" የሚለው የፆታ መደብ የፍትወት ሕዋሳችንን ታሳቢ እና ዋቢ ያደረገ ቢሆንም ነገር ግን አጠቃላይ ስብዕናችንን እንደሚያሳይ ሁሉ በተመሳሳይ "እርሻዎቻችሁ" ማለት "ሴቶቻችሁ" ማለትን ይይዛል፥ እርሻ ዘር የሚዘራበት እንደሆነ ሁሉ ሴትም ዘር ስለሚዘራባት እርሻ ተብላለች። "እርሻችሁንም በፈለጋችሁት ኹኔታ ድረሱ" የሚለው አንቀጽ የወረደበት ሠበቡ አን-ኑዙል መዲና ላይ የነበሩ አይሁዳውያን፦ "ማንም የሚስቱን ሃፍረት በጀርባ በኩል ተራክቦ ያደረገ ልጁ ጠንጋራ ይሆናል" የሚል የተንጋደደ መረዳት ስለያዙ ነው፦
ጃምዒ አት-ቲርሚዚይ መጽሐፍ 47, ሐዲስ 3245
ከጃቢር ኢብኑ ሙንከዲር ሰምቶ እንደተረከው፦ "አይሁዳውያን፦ "ማንም የሚስቱን ሃፍረት በጀርባ በኩል ተራክቦ ያደረገ ልጁ ጠንጋራ ይሆናል" አሉ፥ ከዚያም አላህ፦ "ሴቶቻችሁ ለእናንተ እርሻ ናቸው፥ እርሻችሁንም በፈለጋችሁት ኹኔታ ድረሱ" የሚለውን አንቀጽ አወረደ"።
عَنِ ابْنِ الْمُنْكَدِرِ، سَمِعَ جَابِرًا، يَقُولُ كَانَتِ الْيَهُودُ تَقُولُ مَنْ أَتَى امْرَأَتَهُ فِي قُبُلِهَا مِنْ دُبُرِهَا كَانَ الْوَلَدُ أَحْوَلَ فَنَزَلَتْ : (نِسَاؤُكُمْ حَرْثٌ لَكُمْ فَأْتُوا حَرْثَكُمْ أَنَّى شِئْتُمْ )
"በፈለጋችሁ ሁኔታ" ማለት በጀርባ በኩል ተራክቦ"doggy sex" ማድረግም ክልክል አይደለም ማለትን ይጨምራል፥ ያ ማለት በመቀመጫ በኩል ተራክቦ”anal sex” ማድረግ ይቻላል ማለት እንዳልሆነ ለማሳየት እዛው ዐውድ ላይ፦ "አላህ ካዘዛችሁ ስፍራ ተገናኙዋቸው" በማለት ይናገራል። በመቀመጫ ተራክቦ ማድረግ ሐራም ነው፥ ሐራም ብቻ ሳይሆን ኩፍሩል አስገርም ነው፦
ቁርኣን 2፥222 ንጹሕ በኾኑም ጊዜ አላህ ካዘዛችሁ ስፍራ ተገናኙዋቸው"፡፡
فَإِذَا تَطَهَّرْنَ فَأْتُوهُنَّ مِنْ حَيْثُ أَمَرَكُمُ اللَّهُ
ጃሚዒ አት-ተርሚዚ : መጽሐፍ 1, ሐዲስ 135
አቢ ሁረይራህ”ረ.ዐ” እንዳለው፦ “ነቢዩ”ﷺ” እንዲህ ሲሉ ሰምቻለው፦ ማንም በሓይድ ላይ ካለች ሴት ወይም በመቀመጫዋ በኩል ተራክቦ ቢያደርግ በሙሐመድ”ﷺ” ላይ በተወረደው ክዷል"።
عَنْ أَبِي هُرَيْرَةَ، عَنِ النَّبِيِّ صلى الله عليه وسلم قَالَ ” مَنْ أَتَى حَائِضًا أَوِ امْرَأَةً فِي دُبُرِهَا أَوْ كَاهِنًا فَقَدْ كَفَرَ بِمَا أُنْزِلَ عَلَى مُحَمَّدٍ صلى الله عليه وسلم ”
እዚህ ድረስ ከተግባባን የጴጥሮስ ተማሪ የሮሙ ክሌመንት ሴት እርሻ እንደሆነች አበክሮ እና አዘክሮ ይናገራል፦
ቀለሜንጦስ 10፥50 "አንቲ ገራህት ዕቀቢ ርእሰኪ! ወኢትደምሪ ዘርአ ነኪር፥ እንዘ ሁሉ ዘይናዝዘኪ ሐዘነኪ ሶበ ከመዝ ዘርእኪ ቡሩክ ውእቱ"።
ትርጉም፦ "አንቺ እርሻ ራስሽን ጠብቂ! ሌላ ዘርን አትጨምሪ፥ የሚያጽናናሽ እና ከሐዘንሽ የሚያረጋጋሽ ባልሽ ብቻ ነው"።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የአዲስ ኪዳን መጽሐፍት ቀኖና 35 ናቸው፥ የአዲስ ኪዳን መደበኛ የቀኖና መጽሐፍት 27 ሲሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መጽሐፍት ተጨማሪ ቀኖና 8 ናቸው። ከስምንቱ አንዱ "መጽሐፈ ቀለሜንጦስ" ነው፥ እና ቀለሜንጦስ ሴትን እርሻ ሲል ሞፈርና ቀንበር አዋዶ የሆነው የጓሮ አትክልት አሊያም ሰብል ናት ማለቱ ነውን? በጣም ስመ ጥርና ገናና የአዲስ ኪዳን አራት እደክታባት መካከል ኮዴክስ ኤፍራኤሚ(ኤፍሬም) ሲሆን በ 450 ድኅረ ልደት ያዘጋጀው ሶርያዊው ኤፍሬም ነው፥ ይህ የሶርያ ኤጲጵ ቆጶስ ድንግል ማርያምን እርሻ እንደሆነች አስረግጦ እና ረግጦ በውዳሴም ማርያም ላይ ይናገራል፦
ውዳሴ ማርያም ዘማክሰኞ ቁጥር 4
"አንቲ ውእቱ ገራህት ዘኢተዘርአ ውስቴታ ዘርእ፥ ወጽአ እምኔኪ ፍሬ ሕይወት"።
ትርጉም፦ "ዘር ያልተዘራባት እርሻ አንቺ ነሽ፥ የሕይወት ፍሬ ከአንቺ ወጣ"።
እዚህ ዐውድ ላይ "ዘር" የተባለው የወንድ የዘር ሕዋስ ነው፥ ድንግል ማርያም ኢየሱስን ስትፀንስ የወንድ የዘር ሕዋስ የሌለው ቢሆንም በተፈጥሮዋ የወንድ የዘር ሕዋስ የሚዘራበት ማኅፀን ስላላት "እርሻ" ተብላለች። እና ድንግል ማርያም ሞፈርና ቀንበር አዋዶ የሆነው የጓሮ አትክልት አሊያም ሰብል ናትን? እሩቅ ሳንሄድ አማንያን እርሻ ተብለዋል፦
1 ቆሮንቶስ 3፥9 እናንተ የእግዚአብሔር እርሻ ናችሁ”*፤ you are God’s field. NIV
መልሳችሁ፦ "ውይ ወሒድ ደግሞ ይህ ቀላል ነገር እኮ ነው፦ "እርሻ ናችሁ" ሲለን "የጓሮ አትክልት ናችሁ" ማለት ሳይሆን ልባችን በእርሻ ተመስሏል፥ ቃሉ ደግሞ በዘር ይመሰላል። ይህ እንዴት አይገባህም?" ትላላችሁ፥ ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ ነገር ነው። ከላይ ያለውንም በዚህ ቀመር ተረዱት! "አመድ በዱቄት ይስቃል" እንዲሉ የአሏህ ንግግር ላይ ስትስቁ እና ስትሳለቁ ትውፊት ላይ ሴት እርሻ እንደሆነች ኩልል እና ጥርት ብሎ ተቀምጧል። ለነገሩ ባይብል እና አዋልድ ሴት "ደካማ ፍጥረት ናት፥ በተፈጥሮዋ ደካማ ናት፥ የሰማችውን ሁሉ ሳታመዛዝን አሜን ብላ ትቀበላለችና" ይለናል፦
1 ጴጥሮስ 3፥7 እንዲሁም፥ እናንተ ባሎች ሆይ፥ ደካማ ፍጥረት ስለ ሆኑ ከሚስቶቻችሁ ጋር በማስተዋል አብራችሁ ኑሩ፤
ቀለሜንጦስ 2÷14 ሴት በተፈጥሮዋ ደካማ ናት፤ የሰማችውን ሁሉ ሳታመዛዝን አሜን ብላ ትቀበላለችና።
አሏህ ሂዳያህ ይስጣችሁ! ለእኛም ጽናቱን ይስጠን!
✍ከዐቃቢ ኢሥላም ወሒድ
https://t.me/Wahidcom
ወሠላሙ ዐለይኩም